11/04/2026
🚨 ሰበር እና ልብ ሰባሪ | የሞራል ኪሳራችን ማሳያ፡ ለ35 ዓመታት ሀገር ያገለገሉት አንጋፋ ባለሙያ በአደባባይ ተደበደቡ!
ይህ የአሁኑ ትውልድ ምን ያህል የሞራል፣ የስነምግባር እና የግብረገብነት ክሳራ ውስጥ እንደገባ የሚያሳይ እጅግ አሳዛኝ እና ፀያፍ ድርጊት ተፈፅሟል። የዚህ ልብ ሰባሪ ክስተት ሰለባ የሆኑት አቶ ዋቆ ከዲር የተባሉ አንጋፋ የጤና ባለሙያ ናቸው። እኚህ የዕድሜ ባለፀጋ አገልግሎታቸውን በክብር አጠናቀው የጡረታ መብታቸውን ለማስከበር ሰነዶቻቸውን በማደራጀት ላይ እያሉ፣ በባሌ ሮቤ ከተማ መናኸሪያ ውስጥ ማንነታቸው ባልታወቁ ወጣቶች አሰቃቂ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል።
አቶ ዋቆ ከዲር ለ35 ተከታታይ ዓመታት በቄለም ወለጋ ሆስፒታል፣ በጎባ ሆስፒታል፣ በጊኒር ሆስፒታል እና በራይቱ ጤና ጣቢያ ህዝባቸውን ሲያገለግሉ የቆዩ ውድ የሀገር ባለውለታ ናቸው። ህይወት አድነው፣ በሽተኛ አስታመው እና ሀገርን በታማኝነት አገልግለው ለጡረታ ሲበቁ፤ የህይወት ዘመን ድካማቸው ሽልማት በአደባባይ መደብደብ እና መዋረድ መሆኑ የደረስንበትን የህሊና መሞት ፍንትው አድርጎ ያሳያል።
ይህንን ዘግናኝ ድርጊት የፈፀሙት ወጣቶች ከሌላ ፕላኔት የመጡ ሳይሆኑ፣ የዚሁ ማህበረሰብ እና ስርዓት ውጤቶች ናቸው። ህግ በማይከበርበት ማህበረሰብ ውስጥ ህግ የማያከብር ትውልድ መፈጠሩ የፀሀይ ብርሃን ያህል ግልፅ ነው። የሞራልና የስነምግባር ተቋማት የራሳቸውን ኃላፊነት መወጣት ሲያቅታቸው፤ ጨካኝ፣ ለማንም የማይገደው፣ እጅግ ራስ ወዳድ እና የሞራል ስብእና የጎደለው አመፀኛ ትውልድ መፈጠሩ የማይቀር እውነት ነው።
ለዚህ አሳሳቢ የትውልድ ውድቀት ደግሞ ቤተሰብ፣ ጎረቤት፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የፖለቲካ መሪዎች እና የሃይማኖት አባቶች በሙሉ ተጠያቂዎች ናቸው። በጥቂት መልካም ሰዎች ብንፅናናም፣ ከአገር ጫፍ እስከ ጫፍ እየታየ እና እየተሰማ ያለው የሞራል ስብራት ግን ሀገርን ወደ ባሰ አዘቅት ከመክተቱ በፊት ሁላችንንም ሊያነቃን ይገባል።